በባሃኢ ሃይማኖት በተለይ አንድ መወሳት የሚገባው ነገር አለ። ይኸውም የቅስና ሥርአት አለመኖር ነው። ለአስተማሪዎች ወጭ በበጎ ፈቃድ መዋጮ ማድረግ ይፈቀዳል። ብዙዎችም ጊዜያቸውን በሙሉ ለሃይማኖቱ በመሥራት ያውላሉ። ሆኖም ባሃኢዎች በሙሉ እንዳጋጠማቸውና እንደየችሎታቸው መጠን በማስተማርና በመሳሰሉትም ሥራዎች ተከፋይ መሆን ይገባቸዋል። ለዚህም የቀሳውስትን ተግባር በማከናወንና የተለየ ሥልጣን በመያዝ ከምዕመናን ወገኖቻቸው የተለዩ ክፍሎች የሉም።
በቀድሞ ዘመን ሰዎች መሃይምናንና ያልተማሩ ስለነበሩ እንዲሁም ለሃይማኖት ሥርዓት አከባበርና ስለሕግም አመራር እርዳታን ስለሚፈልጉ ቀሳውስት አስፈላጊ ነበሩ። አሁን ግን ጊዜው ተለውጦ ትምህርት በመላው ዓለም ተስፋፍቷል። ከዚህም በላይ የባሃኦላህ ትዕዛዝ በሥራ ላይ ከዋለ በመላው ዓለም የሚገኙት ወንዶችና ሴቶች ልጆች በቂ ትምህርት ያገኛሉ። በዚህም መሠረት እያንዳንዱ ግለሰብ ቅዱሳን መጻሕፍትን ለራሱ ሊያጠናና የሕይወትን ውሃ ለራሱ በቀጥታ ከምንጩ ሊቀዳ ይችላል። የተለዩ ክፍሎችን ግልጋሎት የሚጠይቅ ከመጠን በላይ የሆነ የሃይማኖት ሥነ ሥርዓትና አከባበር በባሃኢ ሃይማኖት ውስጥ ሥፍራ የለውም። የፍትሕ ሥራም የሚካሄደው ለዚሁ ተግባር በተቋቋሙት ተቋሞች ነው።
ለሕጻን አስተማሪ አስፈላጊ ነው። ሆኖም የአስተማሪው ዓላማ ሕጻኑን ያለአስተማሪ እራሱን እንዲችል፥ በእራሱ ዓይን እንዲያይ፥ በራሱ ጆሮ እንዲሰማና በራሱ አእምሮ እንዲረዳ ማድረግ ነው። እንደዚሁም የሰው ዘር በሕጻንነቱ ዘመን ቄስ አስፈላጊው ነው። ነገር ግን እውነተኛ ተግባሩ ሰዎች ራሳቸውን እንዲችሉ፥ መለኮታዊ ነገሮችን በራሳቸው ዓይን ለማየት፥ በራሳቸው ጆሮ ለመስማትና በራሳቸው አእምሮ ለመረዳት እንዲችሉ ማድረግ ነው። በአሁኑ ዘመን ግን የቄስ ተግባር ተገባዷል። የባሃኢ ትምህርቶችም ዓላማ ይህንን ተግባር ለማገባደድና የሰው ልጆች ከእግዚአብሔር በስተቀር ከማንኛውም ነፃ ሆነው በቀጥታ ወደእርሱ፥ ማለትም ወደ ክስተቱ ፊታቸውን እንዲመልሱ ማድረግ ነው። ሁሉም አንድ ዓላማ ሲኖራቸው የሃሳብ መለያየት ወይንም መደናገር ይቀርና ሁሉም ወደ አንድ ዓላማ ሲያመሩ በበለጠ ለመቀራረብ ይችላሉ።
READ MORE: http://www.bahai.org/
Interesting blog? Like it on Facebook, +1 on Google, Tweet it or share this article on other bookmarking websites.