የኢትዮጵያ ባሃኢዎች
  • የባሃኢ ትምህርቶች
    • አምላክና ሐይማኖቶች
    • የአምላክ መልእክተኞች
    • የባሃኢ ትምህርቶች
    • ህግጋቶችና ደንቦች
    • አስተዳደር
  • ማህበረሰባዊ ተሳትፎ
    • ማህበረሰብ ግንባታ
    • የወጣቶች እንቅስቃሴ
  • የባሃኢ ማህበረሰብ
    • የኢትዮጵያ ባሃኢዎች
    • የአለም ዓቀፍ ማህበረሰብ
    • የባሃኢ ዓለም አቀፍ ማህበረሰብ - አዲስ አበባ ጽ / ቤት
    • ባሃኢዎችን እናስተዋውቃችሁ
  • የባሃኢ መጽሐፍት
    • ቅዱሳን ጽሑፎች
    • ሌሎች
  • ለበለጠ መረጃ
    • ተደጋጋሚ ጥያቄዎች
    • መልእክት ይላኩልን
    • ቪዲዮዎች
  • ENGLISH

የባሃኢ አስተዳደር ምን ማለት ነው?


በባሃኢ ሃይማኖት የሚገኙት የዓለም አስተዳደር ሥርዓቶች የተደነገጉት በባሃኦላህ ሲሆን በሰፊው የተብራሩት በአብዱል-ባሃ ጽሑፎች በተለይም በቃለ ኑዛዜው ውስጥ ነው።

በሃይማኖት አጠቃላይ ባህርይ የአስተዳደር ሥርዓት አወቃቀር ሃይማኖቱ የተቋቋመ በትን መንፈሳዊ ዓላማ ማደናቀፍ የተለመደና እምነቱ ይከተለው የነበረው የእድገት ንዝረቱን ቀጭቶ በዓለም ውስጥ እንዳይሰራጭ ያደርጋል። አስተዳደራዊ መዋቅሩ ሃይማኖቱ የታለመለትን ግብ እንዲመታ መንገድ ወይም መሣሪያ በመሆን ፋንታ በግትርነት የምትክነትን ሚና ይጫወታሉ። የህዝቦች ሰላማዊ ወይም ገንቢ ግንኙነት ሳይኖር በተለያዩ ባህሎች መከፋፈል ለዚህ መንስኤ ሆኗል። በእርግጥም እስካለንበት ዘመን ድረስ የመሠረተውን እምነት የሚመራ የአስተዳደር ስርዓት ግልጽ የሆነ መመሪያ ያስቀመጠ ከቀደምት የእምነት መሥራቾች ውስጥ ማንም አልነበረም። የዚህ ተቋም ዋና ዓላማ በልዩ ልዩ ነገዶች፥ መደቦች፥ ጥቅሞች፥ ባህርያትና እምነቶች መካከል ዘላቂ አንድነትን ለመፍጠር ነው። በዚህ የባሃኢ ዓላማ በኩል የተደረገ ጠለቅ ያለና አስተያየት የተመላ ጥናት በነፍስና በሥጋ መካከል ያለውን ተዋህዶ ያህል የባሃኢ አስተዳደር ሥርዓት ከሃይማኖቱ መሠረታዊ መንፈስ ጋር የተዋሀደ መሆኑን ሊያሳይ ይችላል። የባሃኢ አስተዳደር በባሕርዩ ፥ የኅብረት ሳይንስን ይመስላል። በግብር በመዋል ረገድ ደግሞ በስፋቱ ዓለም አቀፍ የሆነ አዲስና ከፍተኛ ግብረ ገብነትን ይሰጣል።…


የባሃኢ ማኅበራዊ ኑሮ ጥልቅ መሠረትና ሥፋት ያለው በመሆኑ ማንኛውንም ቀና ነፍስ በመቀበል ረገድ ከሌሎች በግል ፈቃድ ከተመሠረቱ ማኅበሮች ይለያል። ሌሎች ማኅበሮች በሃሳብም ባይሆን በግብር፥ በግብ በዓላማም ባይሆን በአፈጻጸም ልዩነትን የሚፈጥሩ ሲሆን የባሃኢ ማኅበር ግን ማንኛውንም ቅን ሰው የወንድማማችነት በሩን ሳይዘጋ ይቀበላል። በማንኛውም ስብሰባ ግልጽ ወይንም ግልጽ ያልሆነ አባሎችን የመምረጫ ዘዴ አለ። በሃይማኖት ይህ የሚሆነው እንደየግል እምነት ክፍሉና እንደአመሠራረት ታሪኩ ነው። በፖለቲካ ይህ የሚፈጸመው በቡድን ወይንም በፓርቲ መካከል ነው። በኤኮኖሚክስ በጋራ ችግር ወይንም በጋራ ኃይል ላይ ይመሠረታል። በኪነ ጥበብና በሳይንስ ይህ ሁኔታ በልዩ ሥልጠና ወይንም እንቅስቃሴ ወይም በዝንባሌ ላይ የተመሠረተ ነው። በእነዚህ ሁኔታዎች ሁሉ የአባል አመራረጥ መሠረቱ እየጠበበ በሄደ ቁጥር እንቅስቃሴው እየጠነከረ የሚሄድ ሲሆን ከባሃኢ ሃይማኖት እንቅስቃሴና ዓላማ ሁኔታ ጋር ግን በፍጹም ተቃራኒ ነው። ስለዚህም እምነቱ ምንም እንኳ የማደግና የመራመድ ኃይል ቢኖረውም ሰዎች በማናቸውም ጉዳይ መከፋፈልንና መለያየትን ስለለመዱ እስከአሁን የንቁ ተከታዮቹን ቁጥር በተመለከተ እድገቱ ዘገምተኛ ነው። ጠቃሚ ሕጎች የመከፋፈል ምክንያቶችና መንገዶች ሆነው ኖረዋል። ከባሃኢ እንቅስቃሴ ውስጥ መግባት ግን እነዚህን ሁሉ ሕግጋት ወደኋላ መተው ነው። በዚህም ጊዜ የተፈጥሮ የግለኝነት ስሜት በዘለዓለማዊው የፍቅር ታላቅ ሕግ ላይ ስለሚያምጽ እራስን ለፈተናና ለችግር ግዴታ መስጠት ማለት ነው። ጠበብቱ ከገጠሬውና ከመሃይምናኑ መቀላቀል አለበት፥ ሃብታሙ ከድኃ፥ ነጩም ከጥቁር፥ መንፈሳዊውም ከዓለማዊው፥ ክርስቲያኑ ከአይሁዱ፥ እስላሙም ከፋርሲው መዋል አለበት። ይህም የሚሆነው የኖሩና ቋሚ የነበሩ አስተያየቶችንና ልምዶችን በማስወገድ ነው።


ሆኖም ይህ ችግር ታላቅ ካሣን ያስገኛል። ኪነጥበብ ከተራው ሕዝብ ሲርቅ እንደሚመክን፥ ፍልስፍናም በግል ሲደረጅ አስተያየት እንደሚጎድለውና ፥ ፖለቲካና ሃይማኖትም ከሰው ዘር ጠቅላላ ፍላጎት ውጭ ከሆኑ ዋጋ ቢስ እንደሚሆኑ እንገንዘብ። ሁላችንም ስለአእምሮአችን፥ ስለግብረ ገብነታችን፥ ስለስሜታችንና ስለህብረተሰባችን እየተከላከልን ስለምንኖር የሰው ጠባይ ገና አልታወቀም። የመከላከል ሳይኮሎጂ ስነ-አእምሮ የማፈን ሳይኮሎጂ ነው። ግን የእግዚአብሔር ፍቅር ፍራቻን ያስወግዳል፤ የፍራቻ መወገድ በውስጣችን ያሉት ድብቅ ኃይሎች ያደረጃል፤ ከሌሎችም ጋር በመንፈሳዊ ፍቅር መዋሀድ እነዚህን ኃይሎች ነፍስ ይዘራባቸዋል። የባሃኢም ኅብረተሰብ በዚህ ዘመን ይህ ሁኔታ በመጀመሪያ ቀስ በቀስ የሚፈጸምበት ነው፤ ይህም ኃይል እየደረጀ ሲሄድ፥ ምዕመናኑም የሰው ልጅ አንድነት አበባ እየፈካ የሚሄድ መሆኑን ሲገነዘቡ በይበልጥ እየተፋጠነ ይሄዳል።…


የአንድን አካባቢ ባሃኢዎች ጉዳይ ማየትና ማስተዳደር የአካባቢ መንፈሳዊ ጉባኤ ተብሎ የሚጠራው ተቋም ኃላፊነት ነው። ይህም ዘጠኝ አባሎች ያሉበት ተቋም በዓመት አንድ ጊዜ ሚያዝያ 21 ቀን በሪዝቫን የመጀመሪያ ቀን ለአካለ መጠን በደረሱ ምዕመናን (ከ21 ዓመት በላይ) ይመረጣል። የምርጫውም ዝርዝር በወጪው መንፈሳዊ ጉባኤ ይዘጋጃል። (ሪድቫን ባሃኦላህ የተገለጸበት ቀን መታሰቢያ በዓል ነው።) ስለዚህ ጉባኤ ሥራና ኃላፊነት አብዱል-ባሃ እንዲህ ሲል ጽፏል፦

“ማንም ምዕመን ከመንፈሳዊ ጉባኤው ጋር ሳይወያይ ምንም ዓይነት የባሃኢ ሥራ ሊሠራ አይፈቀድለትም። ማንኛቸውም ነገር ሥርዓትን የያዘና የተደራጀ ይሆን ዘንድ ምዕመናኑ በልብና በመንፈስ የጉባኤውን ውሳኔ አለአንዳች ቅሬታ መቀበል አለባቸው። ይህ ካልሆነ ግን እያንዳንዱ ሰው በግሉ በመሄድ የራሱን አስተያየትና ምኞት ስለሚከተል ለሃይማኖቱ ጉዳትን ያስከትላል።


“ለሚመካከሩ ሁሉ መሠረታዊና አስፈላጊ ነገሮች የሃሳብ ቀናነት፥ የመንፈስ ንጽሕና፥ ከሁሉም የግል ፍላጎቶች ርቆ የእግዚአብሕርን ብቻ መከተል፥ በመለኮታዊ ማዓዛው መማረክ፥ በምዕመናኑም መካከል ትሕትናና ዝቅተኝነትን ማሳየትና እግዚአብሔርን በማገልገል ላይ በሚደርሰው ረጅም ሥቃይና ችግር መታገስ ናቸው። የእግዚአብሔር ፈቃዱ ሆኖ እነዚህን ጸጋዎች ከታደሉ ከማይታየው የባሃ መንግሥት አሸናፊነት ለእነርሱ ይወርድላቸዋል። በዚህ ዘመን የጉባኤዎች መመካከር አንገብጋቢና እጅግ በጣም አስፈላጊ ነው። ለእነርሱም መታዘዝ አስፈላጊና ግዴታም ነው። አባሎቹ አንዳች ቅሬታና አለመግባባት በማይፈጠርበት መንገድ መነጋገርና መወያየት አለባቸው። ይህም የሚሆነው እያንዳንዱ አባል ሃሳቡን በሙሉ ነፃነት አቅርቦ ምክንያቶቹን በግልጽ ሲደረድር ነው። ማንም ሰው ሃሳቡን ቢቃወም ጉዳዩን አጣርተው እስከተወያዩበት ድረስ እውነተኛው መንገድ ስለማይገለጥ መቀየም የለበትም። የእውነት ብልጭታ የሚታየው ልዩ ልዩ ሃሳቦች ከተጋጩ በኋላ ነው። ከውይይቱ በኋላ አንድ ሃሳብ በሁሉም ከተደገፈ መልካም ነው፤ ግን የእግዚአብሔር ፈቃድ ባይሆንና ልዩነት ቢፈጠር የድምፅ ብልጫ ያገኘው ሃሳብ መጽደቅ አለበት። ...


“የመጀመሪያው ሁኔታ በጉባኤው አባሎች መካከል ፍጹም ፍቅርና ስምምነት መፍጠር ነው። የአንድ ባሕር ውሃ፥ የአንድ ወንዝ ፏፏቴዎች የአንድ ሰማይ ከዋክብት፥ የአንድ ፀሀይ ብርሃን፥ የአንድ ቦታ ዛፎች የአንድ ተክል ሥፍራ አበቦች በመሆናቸው የልዩነትን መንፈስ ማስወገድና የእግዚአብሔርን አንድነት ማሳየት አለባቸው። ፍጹም አንድነትና ስምምነት ከሌለ ያ ስብሰባ መበተን፥ ጉባኤውም እንደሌለ መቆጠር አለበት። “ሁለተኛው ሁኔታ ወደ ስብሰባው በሚመጡበት ጊዜ ፊታቸውን ወደ እግዚአብሔር መንግሥት መመለስና ከእግዚአብሔርም ዕርዳታን መጠየቅ አለባቸው። ... ውይይቱ ነፍስ የምትዳብርበት፥ ሕፃናት የሚማሩበት፤ የድሆች ችግር የሚቃለልበት፤ በዓለም ያሉ በማንኛቸውም ክፍል የሚገኙ ድኩማን የሚረዱበት፤ ለሰው ሁሉ ችሮታ የሚደረግበት፤ የእግዚአብሔር መዓዛ የሚሰራጭበትና ቅዱስ ቃሉ የሚስፋፋበትን የመሳሰሉ መንፈሳዊ ጉዳዮችን የሚመለከት መሆን አለበት። እነዚህን ሁኔታዎች ለማሟላት ከቻሉ የመንፈስ ቅዱስ ፀጋ ይወርድላቸውና ጉባኤው የመለኮታዊ ቡራኬ ማዕድ ይሆናል። የሰማይ መላእክት ለእርዳታ ይደርሱላቸዋል። በየዕለቱም በአዲስ መንፈስ ይሞላሉ።”


ሾጊ ኤፌንዲ ይህንኑ በማብራራት የሚከተለውን ጽፏል፦
“... ከምዕመናን ማንም ቢሆን የአካባቢው መንፈሳዊ ጉባኤው ካልተነጋገረበትና ካላጸደቀው በስተቀር ለሕዝብ ምንም ዓይነት ነገር ሊሰጥ አይፈቀድለትም። ነገር ግን ጉዳዩ በአገሪቱ በሙሉ ያለውን የባሃኢ እንቅስቃሴ የሚመለከት ከሆነ የአካባቢው መንፈሳዊ ጉባኤ የተለያዩ መንፈሳዊ ጉባኤዎችን ወደሚመለከተው ብሔራዊ መንፈሳዊ ጉባኤ ለውይይትና ለውሳኔ መምራት ያስፈልገዋል። በአካባቢው ጽሑፎችን ሕትመት ጉዳይ ብቻ ሳይሆን ማንኛውም በአካባቢው ሃይማኖቱን የሚመለከት ነገር ለአካባቢው መንፈሳዊ ጉባኤ በግልም ሆነ በጋራ መቅረብ አለበት። ይህም መንፈሳዊ ጉባኤ ጉዳዩ ብሔራዊ ካልሆነ በቀር ውሳኔ ይሰጥበታል፤ ከሆነ ግን ወደ ባሃኢ ብሔራዊው መንፈሳዊ ጉባኤ ያስተላልፋል። ይህም ብሔራዊ መንፈሳዊ ጉባኤ ጉዳዩ በብሔራዊ ወይንም በአካባቢ ደረጃ የሚፈጸም መሆን አለመሆኑን የመወሰን ኃላፊነት አለበት። (ብሔራዊ ጉዳይ ሲባል ፖለቲካን የሚመለከቱ ጉዳዮችን አይደለም። ምክንያቱም በዓለም ያሉ የእግዚአብሔር ምዕመናን በሙሉ በምንም ዓይነት ፖለቲካ ውስጥ እንዳይገቡ ተከልክለዋል። ስለዚህ ይህ ብሔራዊ ጉዳይ በአገሩ የሚኖሩ የምዕመናንን መንፈሳዊ ጉዳይ ብቻ የሚመለከት ነው።)


“የሃይማኖቱ አንድንነት፥ የምዕመናኑ ኅብረት እንዲጠነክርና የፍቁራኖቹም መንፈሳዊ ሥራ ይፋጠን ዘንድ በልዩ ልዩ መንፈሳዊ ጉባኤዎችና በአባሎቻቸውም መካከል በተለይም በእያንዳንዱ የአካባቢ መንፈሳዊ ጉባኤና በአባሎቻቸውም መካከል እንዲሁም በእያንዳንዱ የአካባቢ መንፈሳዊ ጉባኤና በብሔራዊው መንፈሳዊ ጉባኤ መካከል ሙሉ ስምምነትና ኅብረት በጣም አስፈላጊ ነው። …


“በእነዚህ ልዩ ልዩ የአካባቢና የብሔራዊ ጉባኤዎች ላይ ነው የወደፊቱ ዓለም አቀፍ ቤተ ፍትሕ ተቋም ተጠናክሮ የሚመሠረተው። እነዚህ ተቋማት በአንድነት ተጠናክረውና ተስማምተው እስኪቋቋሙ ድረስ የዚህ የሽግግር ዘመን ፍጻሜ ተስፋ አይኖረውም...።

“... የእግዚአብሔር ሃይማኖት መሠረታዊ እውነት ትሁት ስብዕና እንጂ አስገዳጅ ሥልጣን ወይም የበላይነት አለመሆኑን በአእምሯችሁ ተገንዘቡ። ገደብ የሌለው ሥልጣን ሳይሆን ግልጽና ፍቅር የተመላበት የውይይት መንፈስ ነው። የምኅረትን፥ የፍትህን፥ የነፃነትንና የታዛዥነትን፥ የእያንዳንዱ መብት ቅድስናና የእራስን ማሸነፍ፥ የንቃትን፥ የግል አስተያየትና ጥንቃቄ፥ የወንድማማችነት፥ የጀግንነትና የብርታትን ዓላማ የሚያስማማ ከእውነተኛ ባሃኢ መንፈስ በስተቀር ከቶ ሌላ ነገር የለም።”

የአንድ አገር የአካባቢ መንፈሳዊ ጉባኤዎች በሌላ ዘጠኝ የተመረጡ አባሎች በሚገኙበት ብሔራዊ መንፈሳዊ ጉባኤ በሚባል ተቋም አማካይነት የተሳሰሩና የተገናኙ ናቸው። ይህ ተቋም የሚመሠረተው በአካባቢው ባሃኢዎች በተመረጡ ወኪሎች በዓመት አንድ ጊዜ በሚደረገው ምርጫ ነው። ... ወኪሎቹ የሚመረጡት አንድ መንፈሳዊ ጉባኤ በተቋቋመበት አካባቢ በሚኖሩ ለአካለ መጠን በደረሱ ምዕመናን ነው። በብሔራዊው ስብሰባ ውስጥ የሚገኙት ወኪሎች ቁጥር የሚወሰነው በሚወክሏቸው ምዕመናን ብዛት ነው። ... ይህ ብሔራዊ ስብሰባ የሪዝቫን በዓልን ምክንያት በማድረግ ቢከናወን ይመረጣል። የሪዝቫን በዓል ባሃኦላህ በባግዳድ አጠገብ ሪድቫን በምትባል አትክልት ሥፍራ ትምህርቱን ያወጀበት ከሚያዝያ 21 ቀን ጀምሮ ያሉት ተከታታይ 12 ቀናት ናቸው። ለወኪሎች እውቅና የመስጠት ሥልጣን የወጪው ብሔራዊ መንፈሳዊ ጉባኤ ነው።


የብሔራዊ ስብሰባ ዋና ዓላማ እያንዳንዱ የባሃኢን እንቅስቃሴ እንዲረዳ ለማድረግና የአለፈውን ዓመት የአካባቢውንና የብሔራዊውን የሥራ ፍሬ ዘገባ ለመስማት ነው። የባሃኢ ወኪል ተግባር በብሔራዊው ስብሰባ መካፈልና የብሔራዊ መንፈሳዊ ጉባኤን አባሎች በመምረጥ ብቻ የተወሰነ ሳይሆን በስብሰባው ላይ በአሉ ጊዜ ወኪሎቹ ለአዲሱ ብሔራዊ መንፈሳዊ ጉባኤ ሃሳብ አቅራቢዎችና አማካሪዎች ሲሆኑ የብሔራዊ መንፈሳዊ ጉባኤው አባሎችም የቀረበውን ሃሳብ በጥንቃቄ መመልከት አለባቸው። …

ብሔራዊ መንፈሳዊ ጉባኤ ከአካባቢው መንፈሳዊ ጉባኤዎችና በጠቅላላው አገሩ ውስጥ ከሚገኙ ምዕመናን ጋር ያለው ግኑኝነት ምን መምሰል እንዳለበት በሃይማኖቱ ሞግዚት፥ በሾጊ ኤፌንዲ እንደሚከተለው በደብዳቤዎቹ ተገልጧል፦


“የአገሩ ሁኔታ ምቹና የምዕመናኑም ቁጥር በርከት ያለ ከሆነ... በማንኛውም ሀገር ምዕማናኑን የሚወክል ‘ብሔራዊ መንፈሳዊ ጉባኤ’ ወዲያውኑ ማቋቋም እጅግ አስፈላጊ ነው።


“አስፈላጊነቱም የምዕመናኑና የአካባቢው መንፈሳዊ ጉባኤዎች አያሌ ግዴታዎቻቸውን ከዚህ ተቋም ጋር በመመካከር እንዲፈጽሙ ለማነቃቃት፥ ለማዋሀድና ለማስተባበር ነው። ከቅድስት ሀገርም ጋር የቅርብ ግንኙነት በማድረግ አንዳንድ አስፈላጊ እርምጃዎችን ለመውሰድና በሀገሩ ውስጥ የሃይማኖቱን ጉዳይ ለመምራት ነው።


“ሌላም ከመጀመሪያው ያላነሰ ኃላፊነት ወይም ሥራ አለበት። ከጊዜ በኋላ በአብዱልባሃ ኑዛዜ ‘ሁለተኛው ቤተ ፍትሕ’ በተባለው መሠረት የብሔራዊ ቤተ ፍትሕ ስለሚሆን በኑዛዜው ግልጽ ትዕዛዝ መሠረት ከሌሎች የባሃኢ ዓለም ብሔራዊ መንፈሳዊ ጉባኤዎች ጋር በመተባበር በዓለም በሙሉ የሃይማኖቱን ጉዳይ የሚመለከተውን፥ መመሪያ የሚሰጠውን - የሚያደራጅና የሚያዋህደውን የታላቅ ሸንጎና የዓለም አቀፍ ቤተ ፍትሕ አባሎችን ይመርጣል።…

“የዓለም አቀፍ ቤተ ፍትሕ እስኪቋቋም ድረስ በዓመት አንድ ጊዜ የሚመረጠው ይህ ብሔራዊ መንፈሳዊ ጉባኤ በሥሩ በሚተዳደሩ የአካባቢ መንፈሳዊ ጉባኤዎች ላይ ሙሉ ሥልጣን ስላለውና የምዕመናኑን ሥራ መመሪያ መስጠትና ሃይማኖቱን በንቃት መጠበቅ፥ እንቅስቃሴውንም በጠቅላላው ማየትና መቆጣጠር ተግባሩ ስለሆነ በርግጥም ታላቅ ሃላፊነት አለበት።


“ሃይማኖቱን የሚመለከቱ፥ ትርጉምና ሕትመትን፥ ማሽሩል አዝቃርና የማስተማር ሥራን ሌሎችም ከአካባቢ ጉዳይ ለየት ያሉ ዋና አስፈላጊ ጉዳዮችን ሁሉ በብሔራዊው መንፈሳዊ ጉባኤ ሥር መሆን አለባቸው። “እነዚህን የመሳሰሉትን ጉዳዮችንም እንደአካባቢው መንፈሳዊ ጉባኤ ሁሉ በሀገሩ ውስጥ ከሚገኙ ምዕመናን መካከል ብሔራዊ መንፈሳዊ ጉባኤ ለሚመርጣቸው ልዩ ኮሚቴዎች መምራት አለበት። የአካባቢ ኮሚቴዎች፥ በአካባቢው መንፈሳዊ ጉባኤ እንደሚተዳደሩ ሁሉ እነዚህም ኮሚቴዎች በብሔራዊ መንፈሳዊ ጉባኤው ሥር ይተዳደራሉ።


“የብሔራዊ መንፈሳዊ ጉባኤው፥ አንድ ጉዳይ፥ አካባቢውን የሚመለከት ወይንም አጠቃላይ የሀገሩ ጉዳይ መሆን አለመሆኑን መወሰን፥ ቢያስፈልግ ጉዳዩን እራሱ መመልከት አለበለዚያም የአካባቢው መንፈሳዊ ጉባኤ እንዲወስን ማድረግ አለበት።…


“... የምንወደውና የምናገለግለውን የሃይማኖቱን ጉዳይ ለማስቀደም እንዲቻል አዲስ ገቢው ብሔራዊ መንፈሳዊ ጉባኤ አንዴ ስብሰባው ላይ በተገኙት ወኪሎች ከተመረጠ በኋላ የወኪሎችን የጋራም ሆነ የግል ምክርና አስተያየት እንዲሁም ምኞት አጥብቆ ማስተዋል የተቀደሰ ተግባሩ ነው። ምስጢራዊነትን፥ ተገቢ ያልሆነ ዝምተኛነትንና አምባገነናዊ ስሜት ከመካከላቸው ፈጻሚ በማጥፋት ለመረጧቸው ወኪሎች ዕቅዳቸውን፥ ተስፋቸውንና ስሜታቸውን በደስተኝነትና በሰፊው ማብራራት አለባቸው። በአዲሱ ዓመት ሊፈጸሙ የታቀዱትን ጉዳዮች ለወኪሎቹ ማስታወቅ፥ የእነርሱንም ሃሳብና አስተያየት በፀጥታና በእርጋታ ማጥናትና መመዘን አለባቸው። አዲሱ ብሔራዊ መንፈሳዊ ጉባኤ ስብሰባው በመካሄድ ላይ እንዳለና ስብሰባውም ከተጠናቀቀ በኋላ መግባባት የሚፈጠርበትን፥ ሃሳብ ለሃሳብ የመለዋወጥ ዘዴ የሚደረጅበትንና የሚቻልበትን፥ መተማመን የሚጠነክርበትን እና የሚፈጠርበትን፥ብልሃትና መንገድ መፈለግና ይህን የጋራ ዓላማ ለማገልገል ያላቸውን ፈቃደኝነት በማንኛቸውም አጋጣሚ መግለጽ አለባቸው። …


“የሆነ ሆኖ ጠቅላላ ጉባኤው ለተከታታይና ረጃጅም የስብሰባ ጊዜዎች ውሱንነት ምክንያት ብሔራዊ መንፈሳዊ ጉባኤው ሃይማኖቱን የሚመለከቱ መሠረታዊ ጉዳዮችን፥ ማለትም አንድ የአካባቢ መንፈሳዊ ጉባኤ በባሃኢ ሕግና አስተዳደር መሠረት የሃይማኖቱን ሥራ መምራቱንና አለመምራቱን የመወሰንን ጉዳይና የመሳሰሉትን በእጁ መያዝ አለበት ... ።”


ዓመታዊ የአካባቢ የባሃኢ ምርጫ በሚደረግበት ጊዜ የምርጫ ዝርዝር የማዘጋጀቱ ጉዳይ የአካባቢው መንፈሳዊ ጉባኤ ኃላፊነት ነው። ሆኖም ለዚህ ጉዳይ መመሪያ ይሆን ዘንድ የሃይማኖቱ ሞግዚት የሚከተለውን ጽፏል፦


“... የጊዜው ሁኔታ እንደሚፈቅደው አንድ ሰው እውነተኛ አማኝ መሆንና አለመሆኑን ለመወሰን የሚቻልባቸው መሠረታዊ ነገሮች ባጭሩ እንደሚከተለው የተነገሩት ናቸው። በአብዱል-በሃ ኑዛዜ እንደታዘዘው የሃይማኖቱን አዋጅ ነጋሪ፥ የሃይማኖቱን መሥራችና የሃይማኖቱን እውነተኛ ምሳሌ ደረጃ ማወቅ ማንኛውንም በብዕራቸው የተገለጸውን አለአንዳች ቅሬታ መቀበልና መፈጸም፥ማናቸውንም የተወዳጁ ኑዛዜ ሃረጎች የሚያዙትን በታማኝነት መፈጸም መከተልና በጊዜው ከሚገኘው የባሃኢ አስተዳደር ተቋምና መንፈስ ጋር ግንኙነት ያላቸው መሆን አለባቸው። እንደዚህ ያለው ቁም ነገር ከመወሰኑ በፊት እነዚህን መሠረታዊና ቋሚ ጉዳዮች በመግባባትና በጥንቃቄ መመርመር ያስፈልጋል።”

አብዱል-ባሃ የባሃኢ ተቋማት ይበልጥ የሚስፋፉበትን መመሪያ ሰጥቷል፦
“እግዚአብሔር ያዘዘው፥ የጥሩ ሁሉ ምንጭ የሆነውና ከስህተት ነፃ የሆነው ቤተ ፍትሕ በጠቅላላው ምዕመናን መመረጥ አለበት። አባሎቹ ፈሪሃ እግዚአብሔር ያደረባቸው፥ የዕውቀት፤ የመግባባት ምንጮች፥ ለሰው ልጅ በጎነት አሳቢዎች መሆን አለባቸው። ይህም ጉባኤ የዓለም-አቀፍ ቤተ-ፍትህ1 ማለት ነው። ይህም ሲሆን በየሀገሩ ብሔራዊ ቤተ-ፍትሆች ተቋቁመው እነርሱ የዓለም-አቀፍ ቤተ- ፍትሕ አባሎችን መምረጥ አለባቸው።


“ማንኛውም ጉዳይ ወደዚህ ተቋም መመራት አለበት። በቅዱሳት መጻሕፍት ውስጥ ያልተገለጹትን ማንኛውንም ደንቦችና ትዕዛዛትን ያወጣል። ለማንኛውም ነገር መፍትሔ የሚሰጥ ይህ ተቋም ነው። የሃይማኖቱም ሞግዚት የዚህ ተቋም የዕድሜ ልክ የተከበረ አባልና የበላይ ኃላፊ ነው። እራሱ በመካከላቸው ተገኝቶ ከምክራቸው ተካፋይ መሆን ቢሳነው አንድ ወኪል መምረጥ አለበት። ... ይህ ተቋም ሕግ ያወጣል፥ ሥራ አስፈጻሚውም ክፍል በተግባር እንዲውሉ ያደርጋል። የዓለም ክፍሎች በሙሉ ገነት እንዲሆኑ በሁለቱ ክፍሎች አንድነትና ስምምነት የትክክለኝነትና የፍትህ መሠረት እንዲጸናና እንዲጠነክር ሕግ አውጭው አስፈጻሚውን መርዳት፥ አስፈጻሚውም ሕግ አውጭውን መርዳት እና መደገፍ አለበት።…


“... ማንኛውም ሰው በታላቁ ቅዱስ መጽሐፍ መመራት አለበት። እዚያም በግልጽ ያልተነገረ ቢኖር ጉዳዩ ወደ ዓለም አቀፍ ቤተ-ፍትሕ መመራት አለበት። ይህ ተቋም በአንድ ድምጽ ሆነ በድምጽ ብልጫ ያፀደቀው ውሳኔ እግዚአብሔር እንዲሆን ያዘዘው ዕውነተኛ ነገር ነው። በዚህም የማይስማማ ሁሉ ግጭትን የሚወድ ተንኮለኛና ከእግዚአብሔር ቃል ኪዳን የራቀ ነው።”

በአሁኑ ጊዜ እንኳን በዓለም የሚገኙ ባሃኢዎች ሁሉ በማያቋርጥ መጻጻፍና በግላዊ ጉብኝት የጠበቀና መተሳሰብ የመላበት ግንኙነት አላቸው። የእነዚህ የልዩ ልዩ ዘሮች፥ ነገዶችና የሃይማኖት ክፍሎች መቀራረብ ባሃኦላህ በመሠረተው የአንድነት መንፈስ ኃይል የከንቱ ጥላቻ ሸክምና የአጋጣሚ ታሪክ ሁኔታ የፈጠረው መከፋፈል ሊሸነፍ ለመቻሉ በቂ ማስረጃ ነው።

Interesting blog? Like it on Facebook, +1 on Google, Tweet it or share this article on other bookmarking websites.

የአስተዳደር ስርዓት

  • መመካከር
  • ቀሳውስት የሌሉበት ሃይማኖት
  • የባሃኢ አስተዳደር ምን ማለት ነው?
  • Follow via Facebook
  • Follow via Youtube
unity

© 2023 የኢትዮጵያ ባሃኢዎች

Go Top