መሠረታዊ የሆኑ የባሃኢ መርሆዎች
የባሃኢ እምነት ከአምላክ የተገለፀና ራሱን የቻለ ሐይማኖት ሲሆን ዓላማው ሁሉንም የሰው ዘሮችና ህዝቦች በአንድ ሁሉን አቀፍ የአምላክ እቅድና ሃይማኖት ለማዋሃድ ነው፡፡ ባሃኡላህ የባሃኢ እምነት መስራች ሲሆን ተከታዮችም ባሃኢዎች ይባላሉ፡፡
በጽሑፎችም ባሃኡላህ እንዲህ ይላል፤-
‹‹ ጌታ ከፍተኛ ፈውስና እጅግ በጣም ታላቅ መሳሪያ አድርጎ ለመላው ዓለም መፈወሻ ያዘዘው የህዝቦቿን በአንድ አለም አቀፋዊ ዓላማ፤ በአንድ የጋራ እምነት ስር መሰብሰብ ነው፡፡ ››
ባሃኦላህ ከጥንት ጀምሮ እንዲመጣ ይጠበቅ የነበረው የሰው ዘር ሁሉ አዳኝ፤ የመላው አለም አደራጅ ፥ የሰው ልጆች አዋሃጅ ፥ ለረጅም ጊዜ ሲጠበቅ የነበረው ሚሌኒየም በር ከፋች ፥ አዲስ “አለምዐቀፋዊ ዑደት” አመንጪ፥ የእጅግ በጣም ታላቁ ሰላም መስራች፥ የእጅግ በጣም ታላቁ ፍትህ ምንጭ፥ የአዲሱ ዓለም ስርዓት ፈጣሪ፥ የዐለም ስልጣኔ ሃሳብ አመንጪና መስራች ፥ ከእርሱ በፊት ከነበሩት ሁሉ የላቀ የአንድ ግሩም ጸጋ መታያ መሆኑን እንዲሁም ወንዞች በውቅያኖሶች ውስጥ እንደሚዋሐዱ ሁሉ ከአሁን በፊት ለነበሩት ሃይማኖቶችም አዋሐጅ መሆኑን ደጋግሞ በግልጽ አስታውቋል። ነቢያት የተነበዩለትና ባለቅኔዎችም ያዜሙለት፤ ሰላምም በምድር ላይ፤ በጎ ፈቃድም በሰዎች መካከል ለተባለው ጊዜ መክፈቻና ለዓለም ሕብረት መነሻ የሚሆን መሠረት ጥሏል።
እውነትን በቅንነት መፈለግ፤ የሰው ልጅ አንድነት፤ በምሥራቅም ሆነ በምዕራብ የሚገኙ ሃይማኖቶች፤ ዘሮችና ሕዝቦች አንድነት፤ የሃይማኖትና የሳይንስ መስማማት፤ የጥላቻና የከንቱ እምነት መደምሰስ፤ የሴቶችና የወንዶች እኩልነት፤ የፍትህና የጽድቅ መቋቋም፤ አንድ ጠቅላይ ዓለም አቀፍ ፍርድ ቤት መቋቋም፤ የቋንቋዎች አንድነት፤ የግዴታ ትምህርትን ማሰራጨት፤ እነዚህና ብዙዎችም እነዚህን የመሳሰሉትም ከ19ነኛው ምዕተ ዓመት የመጨረሻው አጋማሽ በፊት ከባሃኦላህ ብዕር በመፍለቅ ቁጥራቸው ላቅ ባለ መጻሕፍትና መልእክቶች የሰፈሩ ሲሆኑ ከነዚህ መልእክቶች ብዙዎቹ በዚያን ጊዜ ለነበሩት የዓለም ነገሥታትና ገዥዎች የተጻፉ ናቸው።
በመጠኑና በዓላማው ወደር የሌለው መልእክቱ በሚያስገርም አኳኋን ከዘመኑ ምልክትና ፍላጎት ጋር የተስማማ ነው። አዲሶቹ ችግሮች እንደአሁኑ እጅግ የጎሉና የተወሳሰቡ ሆነው ሰውን ከዚህ በፊት ከቶ አልገጠሙትም። ለእነዚህ ችግሮች ማሸነፊያ እንዲሆኑ የቀረቡት አስተያየቶች እንደዚህ ጊዜ በዝተውና ተፋላሽ ሆነው አያውቁም። የአንድ ታላቅ የዓለም መምህር አስፈላጊነት እንደዚህ ጊዜ ጠንክሮ አያውቅም። ምናልባትም ይህን የመሰለው መምህር የመምጣት ምኞት እንደአሁን ጊዜ የተጋነነና የተረጋገጠ ሆኖ ከቶ አያውቅም።
የባሃኦላህ መሠረታዊ የሆኑ መርሆዎች፦
● የሰው ልጅ ዓለም አንድነት
● የተለያዩ የዓለም ሃይማኖቶች መወሃድ
● የሃይማኖትና የሳይንስ መስማማት
● የዓለም ሠላም መመስረት
● የዓለም አቀፍ አስታራቂ ድርጅት መቋቋም
● የዓለም አቀፍ ቤተ ፍትሕ መቋቋም
● የዓለም አቀፍ ቋንቋ መኖር
● የሴቶች ነጻነት መተግበር
● ትምህርት ለሁሉም መዳረስ
● የግልጽ ባርነት ብቻ ሳይሆን የኢንዱስትሪ ባርነትም እንዲወገድ ማድረግ
● የሰው ልጆች መብትና ነፃነት መጠበቅ
READ MORE: http://www.bahai.org/
Interesting blog? Like it on Facebook, +1 on Google, Tweet it or share this article on other bookmarking websites.