የባሃኢ ትምህርት አንድ ወንድ ለአንድ ሴት ጋብቻን ይፈቅዳል። ጋብቻ በሁለቱ ወገኖች መፈቃቀድ እና በወላጆቻቸው ስምምነት ላይ የተመሠረተ እንዲሆን ባሃኦላህ ያዛል። አቅዳስ በተባለው መጽሐፉ እንዲህ ይላል፦
“በእርግጥ ባያን (የባብ ቅዱስ መጽሐፍ) በተባለው መጽሐፍ የተደነገገው ሕግ የሁለቱን (የሙሽራይቱንና የሙሽራውን) ፈቃደኝነት ብቻ የሚጠይቅ ነው። ፍቅርም፥ ወዳጅነትንና የሕዝቡን አንድነት ለመመሥረት ስለፈለግን እንዲሁም ጠላትነትንና መቀያየምን ለማስወገድ ስንል ጋብቻ በወላጆቻቸውም ፈቃደኛነት ጭምር እንዲመሰረት አድርገናል።”
ስለዚህ ጉዳይ አብዱል-ባሃ ላንድ ጠያቂ እንዲህ ሲል ጻፈ፦
“ስለጋብቻው ጥያቄ በእግዚአብሔር ሕግ መሠረት፥ መጀመሪያ ለጋብቻ አንድ ከተመረጠ በኋላ በእናትና በአባት መስማማት ይወሰናል። ከምርጫ በፊት ግን ወላጆች ጣልቃ ለመግባት መብት የላቸውም።” (ታብሌት ኦፍ አብዱል-ባሃ ቮል. 3 ገጽ 563)
አብዱል-ባሃ ሲናገር በዚህ በባሃኦላህ ማስጠንቀቂያ መሠረት በክርስቲያንና በእስላም አገሮች በሚኖሩ ጋብቾች መካከል ተስፋፍቶ የሚገኘው አለመጣጣም በባሃኢዎች ዘንድ ጨርሶ ያልታወቀ ነው። መፍታትም በጣም ያልተለመደ ነው። ስለ ጋብቻ እንዲህ ሲል ጽፏል፦
“የባሃኢ ጋብቻ የሁለቱም ወገኖች ውህደት ሲሆን ሙሉ መስማማትና ፍጹም መፈቃቀር ነው። ቢሆንም ጠባይ ለጠባይ መተዋወቅና ስለ ጉዳዩም በሚገባ ማሰብ አለባቸው። በመካከላቸው ያለው ቋሚ ቃል ኪዳን የዘለዓለም መተሳሰር መሆን ይኖርበታል። ዓላማቸውም ዘላቂ የፍቅር፥ የወዳጅነት፥ የአንድነትና የሕይወት መሆን አለበት…
“የባሃኢ ጋብቻ ሥርዓት ቀላል ነው። የሚያስፈልገው ሙሽራውና ሙሽሪት ቢያንስ በሁለት ምስክሮች ፊት ‘በእውነቱ እኛ ሁላችን በእግዚአብሔር ትእዛዝ እንኖራለን’ ማለት ብቻ ነው። የባሃኢ ጋብቻ በመንፈሳዊ ዓለማት ሁሉ ዘለዓለማዊ አንድነት እንዲኖራቸውና የእርስ በርሳቸውን መንፈሳዊ ኑሮ ያሻሽሉ ዘንድ ተጋቢዎቹ በመንፈስና በአካል አንድ መሆን አለባቸው ማለት ነው። የባሃኢ ጋብቻ ይህ ነው።” (ታብሌት ኦፍ አብዱል-ባሃ ቮል. 2 ገጽ 325)
Interesting blog? Like it on Facebook, +1 on Google, Tweet it or share this article on other bookmarking websites.